/በሚራክል እውነቱ/
በለውጦች መካከል ሰላማችንን ሊያደበዝዙ፣የብልጽግና ጉዟችንን ሊያደናቅፉ የሚችሉ አጋጣሚዎች በየጊዜው ሊፈጠሩ ይችላሉ፡፡ በሁሉም የአገራችን አካባቢዎች የሰላምን አየር ከመተንፈስ ይልቅ ለዘመናት በፍቅር፣ በአንድነት እና በወንድማማችነት የኖረውን ህዝብ ኢላማቸው በማድረግ፤ በህዝብ ጭንብል የራሳቸው ክብርና ዝና ለማግኘት ሲሉ ምክንያት እየፈለጉ አንዱን ብሔር በሌላኛው ላይ ለማስነሳት መሞከር፣በህዝቦች ዘንድ መጠራጠር እንዲፈጠር ማድረግ፣ ፀብ አጫሪ ንግግሮችን መናገር፣አሳሳች ፅሁፎችን መፃፍ፣ትክክለኛ ያልሆኑ ምስሎችን በማህበራዊ ሚዲያዎች መለጠፍ፣ አገር ሰላም ውላ እንዳታድር ፍላጎት የሌላቸውና የግል ጥቅማቸውን ብቻ አስበው የሚሰሩ ሀይሎች ስለመኖራቸው ጥርጥር የለውም፡፡
ሀገሪቱን ለመበታተን የሚጥሩ የእነዚህንና መሰሎቻቸውን ሀላፊነት የጎደለው እኩይ ተግባር ደባ ማጋለጥ ብሎም ከመንግስት ጎን ሆኖ ሀላፊነትን መወጣት ለነገ የማይባል የዛሬ የቤት ስራ ሊሆን ይገባዋል፡፡መልካም ስራዎችን ከማበረታታት ይልቅ ሰበቦችን እየፈለጉ ህዝብን ከህዝብ ለማጋጨት የሚፈልጉ እንቅልፍ አጥተው የሚሰሩ ሀይሎች ዛሬም በጉያችን ውስጥ አሉና፡፡
የህዝብና የሀገር ሰላም ማጣት ለማን በጀ? ችግሮች እንኳ ሲኖሩ ተቀራርበን ለችግሮቹ መፍትሔ ማምጣት ለመንግስት ወይም ለገዢው ፓርቲ ብቻ የሚተው ሳይሆን እያንዳንዳችን የመፍትሔው አንድ አካል እንደሆን ልናስብና የጋራ ምሰሶ የሆነችውን የኢትዮጵያችንን ሰላም በተልካሻ ምክንያት እንዳናጣው ልንረባረብ ይገባል፡፡
ፊትን ወደ ትናንት አዙሮ እንዴት ነው ወደ ነገ መጓዝ የሚቻለው? በእርግጥም ለጥያቄው መልስ መስጠት ያስፈልጋል፡፡በዚህ በሰለጠነ ዘመን አብሮነታችንን ማጎልበት ሲገባን የኋላውን እያነሳን ለፀብ ከተጋበዝን መደማመጥ አቅቶን አንዳችን በሌላችን ላይ ጣታችንን የምንቀስር ከሆነ በእርግጥስ የወደፊቱ እኛነታችን ዕጣ ፈንታ ምን ሊሆን ይችላል፡፡በአንድ ጉዳይ ላይ ተቸንክረን መቆም ለውጥ አያመጣም፡፡ለውጥ ማምጣት የሚቻለው በዛሬው ልፋታችንና ድካማችን ነገን አስበን ስንሰራ መሆኑን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡
አቅጣጫችን ወደፊት ብቻ ነው፡፡ወደ ኋላ እየተመለከቱ እርስ በእርስ መነታረክ ዛሬያችንን ያባክንብናል፡፡የህዝብ ሰላምና የሀገር መረጋጋት ግድ የማይሰጣቸው አንዳንድ ጽንፍ የረገጡ ሀይሎች ወደፊት አስቦ ሀገርን ወደ ተሻለ ከፍታ ከማሻገር ይልቅ በትናንቱ አስተሳሰባቸው ተቸንክረው ይሄው ዛሬ ድረስ በዜጎች መካከል መቃቃርን በመፍጠር ላላስፈላጊ ግጭት፣ግድያና ሞት ምክንያቶች ሆነዋል፡፡
ብልጽግና ፓርቲ ራሱን በአዳዲስ አስተሳሰቦች እየለወጠ ሀገርን ከፈተና ማቅ አውጥቶ ከድህነት ወደ ብልጽግና ማማ ለማሻገር እየታተረ የሚገኝ ህዝባዊ ፓርቲ ነው፡፡ምንጊዜም የኢትዮጵያን ስኬቷን ሳይሆን ውድቀቷን፣ከፍታዋን ሳይሆን የቁልቁለት ጉዞዋን፣ጥንካሬዋን ሳይሆን ድክመቷን የሚመኙ እንቅልፍ የሌላቸው ጠላቶች ህዝቦቿን ሲሻቸው በብሔር አሊያ በሃይማኖት በመከፋፈል የማያባራ የግጭት ቅርቃር ውስጥ ለማስገባት ሲኳትኑ ዛሬም ድረስ ይስተዋላል፡፡
ዳሩ ከፍላጎት የዘለለ መቼም የማይሳካ ሕልም ብቻ ቢሆንም፡፡ይህ መሆን የሚችለው ግን በጋራ ከእኩይ ድርጊታቸው መመከትና መታገል ስንችል ብቻ ነው፡፡ሕዝባችን ለሀገራዊ አንድነት፣ ለሀገር ሰላም፣ ለልማት በጥቅሉ ለሁለንተናዊ ብልጽግና እያሳዬ ያለው ፍላጎት ከጊዚያዊ ግጭቶች ይበልጥ እንደሆነ እንጂ አንሶ አያውቅም፡፡
የኢትዮጵያዊያን የመልማት ፍላጎት ከማንኛውም ከፋፋይ አጀንዳ ይበልጣል፤ይሄ ሐቅ ነው፡፡ ይሄንን ለሺህ ዓመታት ተከባብሮና ተዋዶ የኖረን ጽኑና አስተዋይ ሕዝብ ይዘን ችግሮችን እንዳይደገሙ አድርገን እንደምንፈታቸው ብልጽግና እምነቱ ከፍ ያለ ነው።
ብልጽግና ፓርቲ ከባድ እና ህዝባዊ ሀላፊነትን የተሸከመ ፓርቲ ነው፡፡የተሸከመውን የህዝብ አደራ መወጣት የሚያስችሉ በሳልና ጊዜውን የዋጁ አመራሮችንም ስለመያዙ ጥርጥር የለውም፣ምንም እንኳ በየጊዜው ራሱን መፈተሽ ያለበት ቢሆንም፡፡
ከላይ እስከ ታች ያለው የፓርቲው አመራር ሀገራዊ እሴቶችን በተሟላ መልኩ ለማስቀጠል ትልቅ ኃላፊነት የተሸከሙ ጽኑ አመራሮች ናቸው፡፡በትንንሽ ኮሽታዎች የማይደናገጡ ይልቁንም የተጣለባቸውን ህዝባዊ አደራ ለመወጣትና መስዋዕት ለመክፈል የተዘጋጁና እየከፈሉ ያሉ የአመራሮች ስብስብ ነው-ብልጽግና፡፡
ከሚለያዩንና ለግጭት ከሚያበቁን መንስኤዎች ይልቅ አንድ የሚያደርጉን ብዙ ሺህ ምክንያቶች አሉንና አንድ ሆነን ከውስጥም ሆነ ከውጭ የኛን ትርምስ፣የሀገርን የእርስ በእርስ ግጭት ቆመው ለማየት የሚጓጉ ሀይሎች በአንድነታችን አንገታቸውን ልናስደፋቸው ይገባል፡፡